አትሌት ቀነኒሳ በቀለ ታሪክ ሠራ
በዓለም ሻምፒዮና በ10000 እና በ5 ሺህ በማሸነፍ ለዓለም የመጀመሪያው አትሌት ሆነ
(ተጨማሪ ፎቶግራፎች የታከለበት)

Ethiopia Zare (እሁድ ነሐሴ 17 ቀን 2001 ዓ.ም. August 23, 2009)፦ ኮከቡ አትሌት ቀነኒሳ በቀለ በበርሊኑ 12ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና በ5000 ሜትር አንደኛ በመውጣት ለራሱም ለሀገሩም ሁለተኛውን የወርቅ ሜዳሊያ አግኝቷል። በሻምፒዮናው በአስር ሺህ እና በአምስት ሺህ ወርቅ በማግኘት በዓለም ቀዳሚው አትሌት ሆኗል።
በዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና የረዥም ርቀት ሩጫ ውድድር ታሪክ በ10000 ሜትር እና በ5000 ሜትር አንደኛ በመውጣት ሁለት የወርቅ ሜዳሊያዎች ያገኘ አትሌት የለም። ኮከቡ አትሌት ቀነኒሳ በቀለ በዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ታሪክ የመጀመሪያው አትሌት ሆኗል።
አትሌት ቀነኒሳ ውድድሩን የጨረሰው በ13 ደቂቃ ከ17፡09 ሰከንድ ሲሆን፣ ኢትዮጵያዊው አትሌት ዓሊ አብዶሽ በ13 ደቂቃ ከ19፡11 ሰኮንድ ውድድሩን በስድስተኝነት አጠናቅቋል።
በውድድሩ ኬንያዊው ኤሉድ ኪፕቾጌ ተፎካካሪ ሆኖ የቆየ ቢሆንም ውድድሩን በ5ኛነት አጠናቅቋል። አሜሪካዊው በርናርድ ላጋተ ሁለተኛ፣ የኳታሩ ጄምስ ክዋሊያ ቺኩሩዪ ሦስተኛ፣ የኡጋንዳው ሞሰስ ንዲማ ኪፕሲሮ አራተኛ የወጡ ሲሆን፣ ኤርትራዊው ተክለማሪያም መድኅን ደግሞ ውድድሩን 15ኛ ሆኖ ጨርሷል።
ተጨማሪ ፎቶግራፎች










